ስለ መሬት ነጠቃው ኢህአዴግ “እንወያይ” አለ

Standard

“የሰከነው ትግል” በጋንዲ ምድር ተዘራ

mittal metho

“መጪው ጊዜ በእጃችሁ ነው” የንግግሩ መግቢያ ነበር። “በጨለማ ውስጥ ነን። ከፍተኛ በደል እየተፈጸመብን ነው። ለመረጃ ሩቅ የሆኑ ሰዎች፣ የስልጣኔ ጮራ ያልበራላቸው ሰዎች፣ የመማር ዕድል ያላቸኙ ሰዎች፣ ግፍ እየተፈጸማባቸው ነው። መብታቸውና ሰብዓዊ ክብራቸው ተረግጧል። በጉልበት መሬታቸው እየተነጠቀ በልማት ስም እየተሸጠ ነው። ይህ ሁሉ የሚደረገው በህንድ ህዝብና መንግሥት ስም ነው። ይህ አሳዛኝ ተግባር በስማችሁ እየተከናወነ ነው። በናንተ ስም። ተቃወሙ። ታገሉ። አግዙን። ለዚህ ነው መጪው ጊዜ በእጃችሁ ነው የምለው” ይህ የአዲሲቷ  ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኦባንግ ሜቶ ንግግርና የትግል ጥሪ የቀረበው ህንድ ታዋቂው በሆነው ጃዋሃርላል ኔህሩ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ፊትለፊት ነበር።

“ትግል አርቆ ማሰብ ይጠይቃል፤ እቅድ ይፈልጋል። ትግል ህዝብን ማስተባበርና የረዥም ጊዜ ትልምና ራዕይ ሊኖረው ያስፈልጋል። ስለዚህ ምን እናድርግ? ከየት እንጀምር?” የሚል ጥያቄ የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች አነሱ። አቶ ኦባንግም የሚመሩት ድርጅት ዕቅዱና ራዕዩ በሂደት እዚህ እንዳደረሰው አስረዱ። በቀጣይም ከህንድ ዜጎች ስለሚጠበቀው ዋንኛ ትግል አወሱ። ካሩቱሪ የሚባለው ኩባንያ በኢንቨስትመንት ስም እያከናወነ ያለውን ተግባር ህንዶች ካሳለፉት የቀደመው ችግራቸው ጋር በማያያዝ ተናገሩ። መሃትማ ጋንዲ ገድል ፈጽመው ያለፉበትን ትግል በማድመቅ ይህ ትውልድ የጋንዲን ዓላማ በማንሳት ለወገኖቹ ስቃይ የመድረስ ግዴታና የታሪክ ውርስ እንዳለበት አሳሰቡ። በኢትዮጵያ የሚፈጸመውን የሰብዓዊ መብት ረገጣ በመረጃ ተንትነው አብራሩ።

ኦባንግ “ጥቁሩ ሰው” ወደ ህንድ ያመሩት ከዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ጋር ለመነጋገር አልነበረም። በመጀመሪያ የተገኙት የህንድ ዓለምአቀፍ ማዕከል “Understanding Land Investment in East Africa” በሚል ስያሜ ባዘጋጀው ምክከርና የትግል ልምድ መለዋወጫ መድረክ ላይ ንግግር እንዲያቀርቡ ተጋብዘው ነው። አስቀድሞ በተያዘው ዕቅድ መሠረት በዚህ ስብሰባ ላይ እንዲሳተፉ በጋራ ንቅናቄው የተመረጡ ኢትዮጵያውያንና ሌሎች ግለሰቦች የነበሩ ቢሆንም ከወጪ እና ስፖንሰር አድራጊ ድርጅቶቹ ካጋጠማቸው ሌሎች ተዛማች ችግሮች ምክንያት ሳይሳካ እንደቀረ ተጠቅሷል፡፡

በዚሁ ታላቅ መድረክ ላይ ኦባንግ “ነጻ ስለመሆን የማንንም ፈቃድ አንጠይቅም። ሰው በሰውነቱ የሚከበርበት አገር እስከምንመሰርት ድረስ እንታገላለን። የብሶታችንና የትግላችን መነሻ ለናንተ አዲስ ትግል አይደለም” በማለት የስብሰባውን ቀልብ አነሱት። በህንድ የነጻነት ትግል ውስጥ አብሪ ኮከብ ሆነው የሚኖሩትን መሃትማ ጋንዲን በማስታወስ አገራቸውን ተቀራምተው የነበሩትን የእንግሊዝ የመሬት ቀማኞች እንዴት ድል እንደመቱ አሞካሽተው አቀረቡ። ለጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ ጥያቄ መልስ የሰጡት አቶ ኦባንግ በዩኒቨርስቲው ንግግራቸው ጋንዲን ማጉላታቸው ብቻ ሳይሆን በዩኒቨርስቲ ውስጥ ሌሎች ጋንዲዎች ስለመኖራቸው መናገራቸው ታላቅ ትርጉም የሰጠ እንደነበር ገልጸዋል።

በምክክሩ ላይ የክብር ተናጋሪ የነበሩት የኦክላንድ ተቋም ዋና ዳይሬክተር አኑራድሃ ሚታል “በኢትዮጵያ እየሆነ ያለው ሁሉ በፍጹም ተቀባይነት የለውም” በማለት ምክንያታቸውን አስረዱ። በኢትዮጵያ በወልቃይት ጠገዴ፣ በዋልድባ፣ በአፋር፣ በኦሮሚያ ስለተካሄደው መሬት ንጥቂያና ግፍ የተሞላበት ተግባር በዝርዝር አቀረቡ። የአኑራድሃ ንግግር ህንዶቹን አስደነገጠ።

የህንድ ዓለምአቀፍ ማዕከል ባዘጋጀው በዚህ የምክክርና የትግል ስልት የልውውጥ መድረክ የህንድ ፖለቲከኞች፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች፣ ጋንዲያዊ የትግል መስመር አጥብቀው የሚከተሉ የተለያዩ ፖለቲከኞች፣ የህንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች፣ የገዢው ፓርቲ ተወካዮች፣ የቀድሞ ፖለቲከኞች፣ ተጽዕኖ ፈጣሪ ተሟጋቾች፣ ተለያዩ ማህበራት ተወካዮችና የተለያዩ አካላት የተገኙ ሲሆን ታላላቅ የመገናኛ አውታሮችም ተገኝተዋል።

ዶላር ከዜጎቹ የበለጠበት ኢህአዴግ

“ህወሃት/ኢህአዴግ ዶላር ካገኘ ለሚገባበት ገደል የሚቀርበውን አፋፍ አይመርጥም” በማለት የሚተችበትን ነጥብ ማስታወስ አግባብ ይሆናል። ኢህአዴግ ከስልጣኔ፣ ከወገኖቻቸውና ከዓለም መገናኛ ጀርባ ያሉ፣ በመረጃ ጨለማ ውስጥ የሚኖሩ ምስኪን ዜጎችን በሚዘገንን የንዋይ ፍቅር መብታቸውን እየጨፈለቀ ለመናገር የሚታክት በደል ፈጽሞባቸዋል። አኑራድሃ እንዳሉት “መሬት የመንግስት ነው” በሚል ዜጎችን የግድግዳና ጣሪያ ባለቤት በማድረግ ከቅድመ አያት ሲወርድ ሲዋረድ የመጣውን ሃብታቸውን ዘርፏቸዋል።

ይህ አገር እየመራ እንኳን ራሱን በነጻ አውጪ ስም የሚጠራ ድርጅት በር ዘግቶ በዜጎቹ ላይ የሚፈጽመውን ተግባር በማጋለጥ ቅድሚያ የያዘው የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ (አኢጋን) ነበር። ይህንን አቢይ ተግባር ጊዜ በመውሰድ ያጠናውና በመረጃ በማስደገፍ ስርዓቱ የህዝቦችን ደም እንደሚጠጣ ያጋለጠው አቶ ኦባንግ የሚመሩት ድርጅት ለነዚህ ወገኖች አንደበት በመሆን በዝግ የሚፈጸመውን ርህራሄ የጎደለው ግፍ ይፋ እንዲሆን አደረገ። “እመራዋለሁ” የሚለውን ህዝብ በንዋይ፣ ለዚያውም በዓለም ላይ ታይቶ በማይታወቅ ሂሳብ ድንግል መሬት የሚቸበችበው ህወሓት/ኢህአዴግ በኦሮሚያ አንድ ሄክታር መሬት ከአንድ ዶላር በታች እንደ ጉሊት ጨው መቸርቸሩ ይፋ መሆኑንን ከሰሙ መካከል የኦክላንድ ተቋም ቀዳሚ ሆነ።

በቅርቡ የአማርኛው ትርጉም ይፋ የሚሆነውን “በኢንቨስትመንት ስም የሚፈጸም የመሬት ነጠቃ፤ በኢትዮጵያ” የተሰኘውን ጥናት ያካሄደው የኦክላንድ ተቋም አቶ ኦባንግ ከሚመሩት ድርጅት ጋር በጋራ እየሰራ የሚገኝ ነው፡፡ ይህንንም ጥናት ተግባራዊ ለማድረግና በዘገባ መልክ ለማውጣት ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ያደረገውን አስተዋጽዖ የተቋሙ ዳይሬክተር በአደባባይ የሚመሰክሩት ሲሆን ለጥናቱ የጀርባ አጥንት በመሆን ያሳየውን ዕገዛ ያደንቃሉ፡፡ ተቋማቸው ባደረገው በዚህ ጥናት ኢትዮጵያን አስተዳድራለሁ የሚለው ኢህአዴግ ዜጎቹን ሳያማክርና ፈቃድ ሳይጠይቅ እንደ አሮጌ እቃ በየስርቻው የሚጥል አገዛዝ መሆኑን በማስረጃና በተግባር አራግፈው በአደባባይ ሰቀሉት።

ህንድ እንዴት ተደረሰ?

“የወረቀት ትግል ውጤት የለውም” ሲሉ የሚከራከሩ ነበሩ። አሁንም አሉ። አቶ ኦባንግ ግን በተቃራኒው ይህንን አስተሳሰብ አይቀበሉም። ህንድ አገር ስለመድረሳቸው ዋና ምክንያትና አጋጣሚ ተጠይቀው “ህንድ አገር ባጋጣሚ አልሄድኩም” በማለት መልሳቸውን ይጀምራሉ። በኢትዮጵያ ያለውን ስርዓት የለቀቀ አገዛዝ የሰለቻቸውን ዜጎች ራሳቸውን ነጻ ለማውጣት ድርጅታቸው በየደረጃው ያስቀመጣቸው አካሄዶች እንዳሉ ይናገራሉ። “ህንድ አገር በመሄድ የህዝብ ለህዝብ የተቀናጀ ትግል እንደምናደርግ ያቀድነው አስቀድመን ነው። በዚህ አያቆምም። በእቅዳችን መሰረት እንቀጥላለን” የሚሉት ኦባንግ ሜቶ በኢትዮጵያ የሚካሄደው የመሬት ዝርፊያ ማቆሚያ እንደሚበጅለት በርግጠኛነት ያስረዳሉ። ይህ ግን የድርጅታቸው የመጨረሻ ግብ አይደለም።

ምን ውጤት ተገኘ?

ካሩቱሪ የተባለው ድርጅት በኢትዮጵያ ድንግል መሬት በመውሰድ ቅድሚያ አለው። ይህ ድርጅት የሚጠራው በህንዶች ስም ነው። በህንድ መንግስት በተወሰነ መልኩ የሚደገፍም ነው። በርካታ የአክሲዮን ባለድርሻዎችን ያሰባሰበ ነው። መሰረታዊው የምክክሩ ዓለማ የህንድ ወንድምና እህት ህዝብ እያወቁ እነሱ ታግለው ድል የነሱት የመሬት ዝርፊያ በነሱ ስም በሃያ አንደኛው ክፍለዘመን በኢትዮጵያዊያን ላይ መካሄዱን ማሳወቅ ነበር።

በዚሁ መሰረት ዜጎች ከራሳቸው ምድር ላይ እየተፈናቀሉ፣ እየተገረፉ፣ እየተገደሉ፣ እየተሰደዱ ወዘተ መከራ ሲደርስባቸው እንደነበር የሰሙ አዘኑ። “ይህ በስማችን ስለመደረጉ አናውቅም ነበር” ሲሉ ሃዘናቸውን ገለጹ። አንድ አዛውንት የስብሰባው ተሳታፊ “በኢትዮጵያና በህንድ ህዝብ መካከል ልዩነት የለም። አንድ ነን። ተያይዘን እንታገላለን። ህብረት እንፈጥራለን። ተያይዘን የምንታገልበት አንድ ቀን አሁን ነው” ሲሉ አስተያየት ሰጡ።

“ትግል እቅድ ይጠይቃል። ትግል ህዝብን የማስተባበርና የረዥም ጊዜ ትልም ሊኖረው ይገባል። አሁን ምን እናድርግ? ከምን እንጀምር” የሚል ጥያቄና የትግል ዝግጁነት ተሰማ። ለተከታታይ ቀናት የተካሄደውን ምክክር የህንድ ብሄራዊ ሚዲያዎችና ታዋቂ የዓለም መገናኛዎች ለህብረተሰቡ ይመግቡ ስለነበር፣ በቀጥታ የቴሌቪዥን ውይይት በመደረጉ ካሩቱሪ ተሸበረ።

የህንድ ዜጎች ምን ያደርጋሉ?

“በስማችን ወንጀል ሊሰራ አይገባም። በመንግስት ስም የሰብአዊ መብት ጥሰት ሲካሄድ ዝም ብለን አንመለከትም። መንግስት ለካሩቱሪየሚሰጠውን የገንዘብ ድጋፍ እንዲያቆም፣ የካሩቱሪ ባለ አክሲዮኖች ለዚህ ክፉ ተግባር ተባባሪ ከመሆን ተቆጠቡ” የሚሉና በየደረጃው እየጠነከረ የሚሄድ ማስገደጃ ለማድረግ እንደሚሰሩ ተሳታፊዎቹ አረጋግጠዋል።

ይህ ውሳኔ ባለሃብቱንና ባለ አክሲዮኖቹን በማስጨነቁ የድርጅቱ የባለ አክሲዮኖች ስብሰባ ከመካሄዱ በፊት የሚጀመረው ዘመቻ በጎርፍና በከብት መንጋ ኪሳራ ደርሶበት የነበረውን ኩባንያ በኪሳራ እስከማዘጋት የሚደርስ ትግል እንደሚደረግ ቃል ከማስገባት በላይ ታላቅ ነገር እንደሌለ አቶ ኦባንግ ይናገራሉ። አይያዘውም “የሰከነ ትግል ውጤቱ አሁንም በሰከነ መንፈስ በመከታተል የሚታይ ይሆናል። በዚህ አይበቃም ይቀጥላል። በስሜትና ጊዜያዊ በሆኑ ጥቅሞች ሳንነዳ እቅዳችንና ግባችን በሚያዘን መሰረት እንጓዛለን” ሲሉ ለጎልጉል ተናግረዋል።

መንግስት ለምን ፈራ?

ኢህአዴግ ስብሰባውንና የስብሰባውን ውጤት የፈራው ጥቅሙን ስለሚያጣ ነው። ካሩቱሪ ለቅቆ ሲወጣ ሁሉም መሬት ለመንጠቅ የመጡ ባለሃብቶች በየተራ ይወጣሉ። ይህ ዶላር ፍለጋ የሚምልባቸውን ምስኪን ህዝቦች እየገፋ ያለ ስርዓት ለአፈናው ለሚያወጣው ከፍተኛ በጀት፣ ለተነከረበት ከፍተኛ ሙስናና ዝርፊያ የሚሆን ገቢ ሲያንሰው የራሱ “ሌቦች” ጭምር ስለሚከዱት የህንድ ወገኖች እያሳዩ ያሉት ተቃውሞ ሳይነድና ሳይጠነክር አስቀድሞ ለማስቆም ህወሃት/ኢህአዴግ ሩጫ ጀምሯል።

የጎልጉል የመረጃ ምንጮች እንዳሉት በህንድ አገር የተካሄደው ምክክር በተጠናቀቀበት እለት ከኢትዮጵያ መንግስት በኩል ለኦክላንድ ተቋም ዋና ዳይሬክተር ደብዳቤ ተጽፎላቸዋል። ደብዳቤው ዋና ዳይሬክተሯን ለማነጋገር የሚጠይቅ ሲሆን፣ ጉዳዩም አሁን በተጀመረው ዘመቻ ዙሪያ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል። አቶ ኦባንግ ጉዳዩን አስመልክቶ ለተጠየቁት ሲመልሱ “የመሬት ነጠቃን በተመለከተ ማንኛውም ዓይነት ውይይት አይታሰብም። የተላከው ደብዳቤ ምንም ይሁን ምን አኑራድሃ ስለ ኢትዮጵያ መንግስትና ስለ ቅጥፈቱ ከበቂ በላይ መረጃ ስላላቸው ሊያሳስቷቸው አይችሉም። እኛም በብዙ ፈርጁ ከምናካሂደው ትግል አንዱ በመሆኑ ነቅተን ጉዳዩን እንከታተለዋለን” የሚል መልስ ሰጥተዋል